መጋቢት 26 (04 አፕሪል)
የመድኃኔዓለም ንግሥ በዓል አባ ዲሜጢሮስ፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የምሥራቅ ካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የሌሎችም የምስራቅ ካናዳ አብያተ ክርስቲያን መሪዎች እና ምዕመናን በሚገኙበት በደመቀ ሃይማኖታዊ ሥርዓት ይከበራል።
መጋቢት 27 (05 አፕሪል)
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሆሳዕና በመባል የሚታወቀው እና የኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ኢየሩሳሌም መግባት የሚዘክረው ታላቅ በዓል የሚከበርበት ቀን ነው። ዕለቱ የሁዳዴ ጾም ወደ መጠናቀቂያው መድረሱን እና ህማማት በመባል የሚታወቀው ታላቅ መንፈሳዊ ሳምንት መጀመሪያ መሆኑን ጠቅሰው በዚህ ታላቅ መንፈሳዊ በዐል ላይ ምዕመናን በሙሉ እንዲገኙ የቤተክርስቲያኑ ዋና አስተዳዳሪ መጋቤ ምስጢር ይትባረክ አዳነ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
ሚያዝያ 2 (10 አፕሪል)
ይህ ቀን ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ክርስትና ተከታዮች ጥልቅ የአርምሞና የጸሎት፣ የስግደት ቀን ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ልጆችን ለማዳን የሞተበት፤ የተሰቀለበት ዕለት ነው። በዚህ ስቅለት በሚባለው ዕለት ቤተክርስቲያናችን ለምዕመናን ሙሉ ቀን ለጸሎት ክፍት ሆኖ ይውላል።
ሚያዝያ 4 (12 አፕሪል)
ይህ ዕለት በዓለ ትንሳኤ ወይም ፋሲካ በመባል ይታወቃል። ለኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች በጣም ታላቅ መንፈሣዊ በዓላችን ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን አሸንፎ ከመቃብር የተነሳበት እና የታላቁ ጾም ማብቂያ እለት ነው። በዓሉ ቅዳም ስዑር በሚባለው በትንሳኤ ዋዜማ በምሽት በሚካሄዱ የጸሎት ፕሮግራሞች ተጀምሮ እኩለ ሌሊትን አልፎ የሚጠናቀቅ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት ነው።